Monday, April 8, 2013

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (6)


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!
እንኳን ለብርሃነ ልደቱና ጥምቀቱ አደረሳችሁ፡፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በዓለ ዕረፍትም ረድኤትም በረከት ያሳድርብን አሜን!
ባለፉት ተከታታይ ትምህርታዊ ጹሑፎች አምላክ ልንለው የምንችለው አካል ሊያሟላ ስለሚገባው ባህርያት እያየን እዚህ ደርሰናል፡፡
እግዚአብሔር አምላክ በሁሉ ሥፍራ የሚገኝ አምላክ ነው ስንል ምን ማለታችን ነው? የትኛውም ፍጡር በቦታ በጊዜና በሁኔታ የተወሰነ እንደሆነ የነገረ-መለኮት ሊቃውንትም ሆኑ የፍልስፍና ሊቃውንት ይስማሙበታል፡፡ በምድራውያንም ሆነ ለሰማያውያን ግዙፉንም ይሁኑ ረቂቃን ፍጥረታት በዚሁ የታጠሩ ናቸው፡፡
ሰማያውያን መላእክት እንኳ የልዑሉን ትዕዛዝ ለመፈፀም ሲተጉ አንዱን ሥፍራ ለቀው ወዳንዱ መሔድ ግድ ይላቸዋል፡፡ እንደሪቂቅነታቸው በረቂቅ ከተማ በሦስቱ ሰማያት ኢዮር፣ ራማና ኤረር ወስኖ አስፍሯቸዋል፡፡ ተልኳቸውን ከፈፀሙ በኃላ ወደዚሁ የመላእክት ከተማ ተመልሰው በምስጋና ይተጋሉ፡፡
ለልዑል እግዚአብሔር ግን እንዲህ አይደለም፡፡ አባ ሕርያቆስ በቅዳሴው እንደተናገረው     "ለመለኮት በታች ያለውን ለማንሳት ማጎንበስ ራስንም ማዘንበል ያለበት አይደለም በላይ ያለውን ያወርድ ዘንድ በፊትና በኋላ በቀኝና በግራ ያለውንም ለማቅረብ መዘዋወር የሚያሻው አይደለም፡፡ ሁሉ በእጁ የተያዘ ነው እንጂ" ቅዱስ ዳዊትም " ከመንፈስህ ወዴት እሔዳለሁ፤ ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ ወደ ሰማይ ብወጣ አንተ በዚያ አለህ፤ ወደ ውቅያኖስም ጥልቅ ብወርድም በዚያ ትገኛለህ፤ እንደ ንስር የንጋትን ክንፍ ብወስድ ከአጽናፍ አጽናፍ ብበርም እጅህ በዚያ ትመራኛለች ቀኝህም ትይዘኛለች" በማለት ስለ ልዑል እግዚአብሔር በሁሉ መገኘት ዘምሯል፡፡ መዝ139፥7-10፤ ቅዳሴ ማርያም
ቤተመቅደስን ያነፀ ሰሎሞንም በጌታ እግዚአብሔር ፊት ሲፀልይ…"ሰማያትም ከሰማያትም በላይ ያለ ሰማይ ሊይዙህ አይችሉም፡፡ እንግዲያው እኔ የሠራሁት ቤት እንዴት ያንስ?..."በማለት ገልጾታል፡፡ 1ነገ 8፥27
በኢሳይያስም "ሰማይ ዙፋኔ ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት ለእኔ የምትሠሩልኝ ቤት እንዴት ያለ ነው? ሲል በሁሉ የመላ መሆኑን ገልጿል፡፡ ኢሳ66፡1፤ ማቴ 5፥34
በዘመኑ ፍፃሜ በመጽሐፍ ቅዱስ "በመጀመርያ ቃል ነበር፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበር፤ ቃልም እግዚአብሔር ነበር ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለእርሱ አልሆነም" ተብሎ ልዕልናው ምልዓቱ ስፍሐቱ ከሀሊነቱ የተነገረለት አምላክ "ቃል ሥጋ ሆነ" ተብሎ ትህትናው ተገለጠ፡፡ ምልዓቱን ስፍሐቱን ሳይለቅ ባጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወሰነ፡፡ የሰውን አካልና ባህርይ በመንሳቱ በቦታ በጊዜና በሁኔታ የማይወስነው እርሱ በቦታ በጊዜና በሁኔታ ተወሰነ፡፡ ዮሐ1፥1-14
በቦታ ስንል ፤ በቤተልሔም ተወለደ፣ ወደ ግብፅ ተሰደደ፣ በናዝሬት አደገ፣ወደ ምኩራብ ገባ፣ ወደ  ኢየሩሳሌም ወጣ፣በቀራንዮ ተሰቀለ፣በጎሎጎታ ተቀበረ ወ.ዘ.ተ…ማለት ነው፡፡
በጊዜ ስንል፤ በ12 ዓመቱ ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፣ በ30ዘመን ተጠመቀ እርሱም ራሱ "ጊዜዬ ገና ነው" ብሎ እንደተናገረ የመሳሰሉትን ነው፡፡
በሁኔታዎች፤ ማለት ተፀነሰ፣ ተወለደ፣ ተሰደደ፣ ተራበ፣ተጠማ፣ ተገረፈ፣ ተሰቀለ፣ ሞተ ፣ ተቀበረ ወዘተ… ማለታችን ነው፡፡
ነገር ግን ምንም እንኳ ከላይ ለተጠቀሱት ነገሮች ተገዢ ባይሆንም በፈቃዱ በእውነት በእነዚህ ስር ሆነ፡፡  ያም ሆኖ ግን ለእኛ የለበሰውን ደከማ ሥጋ ብቻ ሳይሆን ኃያል አምላክነቱን ፣አላዋቂ ሥጋን የተዋሀደ ሁሉን አዋቂነቱ፣ ራሱን ባዶ በማድረጉ ውስጥ ያለ ባለጠግነቱን (ሁሉ የእርሱ ከእርሱ በእርሱ መሆኑን) በውሱንነት የተጋለጠ አለመወሰኑን ወዘተ…በሥራውና በቃሉ ገለጠለን፡፡
በማኅፀነ ማርያም ያለተከፍሎ በምልዓት እያለ ሊወሰን ከምልዓቱ አልጎደለም፡፡ በምሳሌ ፀሐይ በጠፈር ሰማይ ሆና ብርሃኗ ወደምድር ሲመጣ በፀሐይቷ ዘንድ በምልዓት አንዳለ ከእኛ ዓይን እንዲዋሃድ፤ ጨለማውን እንደሚገፍ የተሰወረውን እንደሚገልጥ የእርሱም እንዲሁ ነው፡፡ ከሦስተንቱ አልጎደለም  አራት ወደመሆንም አልተጨመረም፡፡ ይህንም በቃሉ ሲያስረግጥ…"ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደሰማይ የወጣ የለም ይኸውም በሰማይ ያለ የሰው ልጅ ነው" ብሏል፡፡ ዮሐ 3፥13 ይህን በተናገረበት ቅፅበት በኒቆዲሞስ ፊት ያለ እርሱ እንደምን በሰማይ ያለ የሰው ልጅ ነው ሊል ይችላል? ምልዓቱን(በሁሉ ቦታ መገኘቱን) ለመግለፅ ካልሆነ በቀር፡፡
ለሐዋርያትና በስሙ ላመን ክርስቲያኖች ሁሉ በገባልን ቃልም እንዲህ ብሏል፡-
ማቴ18፥20 …በስሜ ሁለትና ሦስት ባላችሁበት በመካከላችሁ እሆናለሁ፡፡
ማቴ28፥19… አባቴ አንደላከኝ እኔም እናንተን እልካችኋለሁ፡፡ ሂዱና አህዛብን በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ያዘዘኳችሁንም እያስተማራችሁ ደቀመዛሙርቴ አድርጓቸው፡፡ እነሆ እስከዓለም ፍፃሜ ከእናንተ ጋር ነኝ፡፡
ይልቁንም ቅዱስ ጳውሎስ ለቈላስዩስ ሰዎች በላከው መልዕክቱ " የመለኮቱ ሙላት በሥጋው ተገልጦ ይኖራል " እንዳለ በለበሰው ሥጋ በመለኮታዊ ሥልጣን በአባቱ ዙፋን በአባቱ ክብር ተቀምጦ ራቂቁንም ሆነ ግዙፉን ዓለም የሚታየውንም ሆነ የማይታየውን እንደሚገዛ እንዲሚጠብቅ እንደሚያስተዳድር ገልጿል፡፡ቆላ 2፥9
ዳግመኛም ሲመጣ በክበበ ትስብዕት በግርማ መለኮት ይመጣል፡፡ ይህም ማለት በክበበ ትስብዕት የተወጋ ጎኑ፣ የተቸነከሩ እጆቹ እግሮቹ እየታዩ ይመጣል፡፡ ምንም እንኳ በክበበ ትስብዕት ቢሆንም እነደ አምላክነቱ ሁሉ እኩል ያየዋል፡፡ በኋላ በቀኝ በግራ የሚሆን የለም አንዱ ቀርቦ አንዱ ርቆ አንዱ ከጀርባ አንዱ ከጎን ሆኖ አያያውም፡፡ ለሁሉ በእኩል ከፊቱ ሆኖ ይመለከተዋል አንጂ፡፡ ምን የአዳም ዘር በዝቶ እንደ እንድጽፍቀተ ሮማን ቢጨናነቅ ሁሉ በእኩል ርቀት በአንድ ዓይነት በፊቱ ያየዋል፡፡ ይህም ግዙፍ ሲሆን ረቂቅ ውሱን ሲሆን ምሉዕ አምላክ መሆኑን በተረዳ ነገር ያሳያል፡፡
ልዑል ሲሆን ሳለ ትሁት ሆኖ ራሱን በምንችለው መጠን የገለፀልን፤ ይወዳጀን ዘንድም ፍቃዱ የሆነ ጌትነቱን ፈጣሪነቱን የባህርይ አማላክነቱን አምነን እንመስክር ዘንድ የመረጠን የነገሥታት ንጉሥ የጌቶች ጌታ የአማልክት አምላክ የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ቸር ከሆነ ከሰማያዊ አባቱ አዳኝ ርኅሩኅ ከሆነ ከመንፈስ ቅዱስም ጋር ክብር ምስጋና ይግባው፡፡
ለዘለዓለሙ አሜን!

No comments:

Post a Comment