Monday, April 8, 2013

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (4)


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
       በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!
መግቢያ
        የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን ቻይነቱ በሞት ላይ በነበረው ሥልጣንም ገልጿል፡፡ ሞት የኃጢአት ውጤት(ደመወዝ) ነው፡፡ ለሞት ያልተገዛ ፍጥረትም የለም፡፡ ከአዳም ጀምሮ የአዳማዊው ተፈጥሮ ተጋሪ የሆኑ ልጆቹና ለአዳም የተፈጠሩት ፍጥረቶች ሁሉ በሞት ጥላ ሥር ወድቀዋል፡፡ ርዕሳነ አበው፣ነብያት፣ነገሥታት፣ካህናት፣ሁሉ በሞት መዳፍ ተያዙ ማምለጥም የታቻለው ወይም ይህን የሞት ፍርድ ሊያስቀር የቻለ አንድ ስንኳ አልተገኘም፡፡
ይህንኑ ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ ምዕ 5፥12-21 በጥሩ ሁኔታ አብራርቶታል፡፡ "…ኃጢአት በአንድ ሰው ወደ ዓለም ገባ በኃጢአትም ሞት… ነገር ግነ በአዳም መተላለፍ ምሳሌ ኃጢአትን ባልሠሩት ላይ እንኳ ከአዳም ጀምሮ እስከ ሙሴ ድረስ ሞት ነገሠ…" ጨምሮም "…የኋላኛው ጠላት የሚሻረው ሞት ነው፤ ሁሉን ከእግሩ በታች አስገዝቶአልና፡፡ነገር ግን ሁሉ ተገዝቶአል ሲል ሁሉን ካስገዛለት በቀር መሆኑ ግልጥ ነው" ፡፡ 1 ቆሮ 15፥25-28 በማለት የሞትን ሥልጣንና የሞትን ሥልጣን ሰብሮ ኃያልነቱን(ሁሉን ቻይነቱን) የገለፀውን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥራ ግልፅ አድርጓል፡፡
      አበው ለብዙ ዘመናት ከዚህ የሞት ባርነት ነፃ ሊያወጣቸው ወደሚችል በብዙ ልመና ሲቃትቱ ኖረዋል፡፡ ጊዜው ሲደርስ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ ሞትን ሻረው፡፡ ሞት ነግሦባት በነበረች ምድር ለመጀመርያ ጊዜ " እሰቀላለሁ፣ እሞታለሁ በሦስተኛውም ቀን እነሳለሁ" እንዲሁም " ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል እኔ በፍቃዴ አኖራታለሁ እንጂ ከእኔ ማንም አይወስዳትም፡፡ ላኖራት ሥልጣን አለኝ ደግሞም ላነሣት ሥልጣን አለኝ፤ይህቺን ትዕዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ፡፡" በማለት ሞትን ያስደነገጠ የአዳምን ተስፋ ያረጋገጠ አዋጅ ተሰማ፡፡ ዮሐ 10፥18፣ ማቴ 16፥21
     መግደልና ማዳን የእግዚአብሔር ብቻ ሥልጣን መሆኑ በቅዱሳት መጻሕፍት የተረጋገጠ ነው፡፡ ኦሪ.ዘዳ 32፥39፣ 1ሳሙ 2፥6፣ ማቴ 10፥28-31 ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን "ነፍሴን ላኖራትም ላነሣትም ሥልጣን አለኝ" በማለት በሞት ላይ ያለውን ገዢነቱን በተጨማሪም የመግደልና የማዳን መለኮታዊ ሥልጣን ያለው ወይም እርሱ እራሱ እግዚአብሔር መሆኑን ገለፀ፡፡ ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት በዚያች ሰዓትም የተናገረውን አስተውል፡፡ "ኢየሱስም በታላቅ ድምጽ ጮኾ አባት ሆይ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ አለ፡፡" ይህ ጩኸት ይህ ቃል የሞትን ሥልጣን ያረጋገጠ የዲያቢሎስ መንግስት የቆረጠ ነው፡፡ ሉቃ 23 ፥46
ልዩ ከምትሆን ቅድስት ትንሣኤው በፊትም በኢየሩሳሌም አውራጃዎች እየተዘዋወረ ሲያስተምር ሙታንን በማስነሳት እርሱ በሞት ላይ ፍፁም ሥልጣን ያለው አምላክ መሆኑን አሳይቶናል፡፡
-    ሉቃ 8፥49-56 ፡- ኢያኢሮስ የተባለው የምኩራብ አለቃ ልጁ በሞተችበት ወቅት ጌታችን በቃሉ አስነስቷታል፡፡ "አንቺ ብላቴና ተነሺ" ብቻ በማለት

-    ዮሐ 11፥1-44 ፡- የጌታ ወዳጅ አልዓዛር ሞቶ በተቀበረ በአራተኛው ቀን ጌታችን ትንሣኤና ሕይወት እርሱ መሆኑንና በእርሱ የሚያምን ቢሞትም እንኳ ህያው እንደሚሆን ካወጀ በኋላ ወደመቃብር ሔዶ "አልዓዛር ሆይ ወደ ውጭ ና" በማለት አስነስቶታል፡፡
በዚህ ላይ ምናልባት አንዳንዶች ነቢያት፣ሐዋርያት ድውይ ፈውሰዋል፣ምውት አንስተዋል ይህን አደረጉ ብለን "ሁሉን ቻይ" እንደማንላቸው ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስንም እንዲሁ ነው ብለው ሊከራከሩ ይችላሉ፡፡ 1ኛነገ 17፥17-24፣ 2ኛ ነገ 4፥32-37፣ ሐዋ.ሥራ 9፥40
መልስ
1ኛ- ነቢያትም ሆኑ ሐዋርያት ሙት እስከማንሳት የደረሱት ከልዑል እግዚአብሔር በተሠጣቸው ሥልጣን ጾመው፣ ጸልየው፣ ወድቀው፣ ተነስተው ነው፡፡ ከላይ የተጠቀሱት ጥቅሶች የሚያመለክቱትም ይህንኑ ነው፡፡ ማር16፥17፣ ሉቃ 10፥17-20፣ዮሐ 14፥12-14፡ እውነት እውነት እላችኋለው በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፣ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል… ማናቸውም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ አደርገዋለሁ፡፡ ያለውን ቃልኪዳን ይጠብቅላቸዋል፡፡ የእርሱ ግን መጾም፣መጸለይ፣ መውደቅ፣መነሣት ሳያስፈልገው በሥልጣኑ ነው፡፡
2ኛ- ከነቢያትም ሆነ ከሐዋርያት ሙት እስከማንሳት የደረሱ ሁሉ በመጨረሻ እነርሱ ራሣቸው በሥጋ ሞት ተይዘዋል፡፡ ጌታችን በትንሣኤ ዘጉባኤ እስኪያስነሳቸውም ይጠብቃሉ፡፡ሙት ያስነሱ እነርሱ ለራሳቸው ግን አስነሺ ያስፈልጋቸዋል፡፡ እርሱም ትንሣኤ ሕይወት የተባለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ለእርሱ ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ይህንኑም ለማስረዳት ነው ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት ሰዓት እንኳ ብዙ ሙታን ተነስተው በኢየሩሳሌም የታዩት፡፡ በማቴ 27፥51-54 መላእክትም ለሴቶቹ " ሕያዋን ከሙታን መካከል ስለምን ትሹታላችሁ እርሱ በዚህ የለም ተነሥቶአል" ያሉአቸው፡፡ ሉቃ 24፥6
         በእነዚህ ከብዙ በጥቂቱ አእምሮን ለማንቃትና እምነትን ለማፅናት ከተጠቀሱት በተጨማሪ ብዙ የመፅሐፍት ቅዱስ ክፍሎችና የአበው ትምህርት ሁሉን ቻይነቱን አምልተው አስፍተው ገልፀውታል፡፡ ያን በማንበብና በማስተዋል የበለጠ መጠቀም ያስፈልጋል፡፡ በሚቀጥለው አምላካዊ ባህርያት ከሆኑት "ሁሉን አዋቂ" ስለመሆኑ ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም እንማራለን፡፡
ይቆየን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ጥቅምት 2005

No comments:

Post a Comment