Friday, April 12, 2013


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!
"…ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፤ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና"ፊልጵ 5፥23
በተለያዩ አህጉር ተበትናችሁ በቃሉ ለመኖር ለምትጋደሉ የመንፈስ ልጆቼ የተላከ ህሊናን ሁሉ የሚያልፍ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሰላም ከሁላችሁ ጋር ይሁን!
·   ስለ ዕለተ ሞትህ(ሽ) አስበህ(ሽ) ታውቃለህ? ለመሞትህ(ሽ) ምን ያህል እርግጠኛ ነህ(ሽ)?
·   በሞትህ ጊዜ ምን ዓይነት ሒደቶች ይጠብቁኛል ብለህ(ሽ) ታምናለህ?
·   ጌታ ክርስቶስን ከመናፈቅህ(ሽ) የተነሣ ሞትን ተመኝተህ(ሽ) ታውቃለህ?
·   በዚህች ቅጽበት ለመሔድ (ሞትን ለማስተናገድ) ዝግጁ ነህ(ሽ)? አዎን! ምክኒያት 
አይደለሁም- ምክኒያት

 
   የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቼ ወደ አጠቃላይ ንባቡ ከመሔዳችሁ በፊት ከላይ ለቀረቡት ጥያቄዎች መንፈሳችሁን ለራሳችሁና ለቅዱስ እግዚአብሔር ታማኝ በማድረግ በጹሑፍ መልስ ስጡ፡፡ በመልሳችሁ እርግጠኛ ስትሆኑ ቀሪውን ታነቡ ዘንድ ተፈቅዷል፤መታዘዝ በዚህ አለ!
   በመጽሐፍ ቅዱስ ከምናነባቸው አስደማሚ ነገሮች አንዱ ይኸው የቅዱሳን ናፍቆት ነው፡፡ በዚህ ከዚህ ዓለም የመለየት የቅዱስ ጳውሎስ ናፍቆት ሌሎችም ቅዱሳን ተባብረውበታል፡፡ ክቡር ዳዊት "ዋላ ወደ ውኃ ምንጭ እንደሚናፍቅ፤አቤቱ እንዲሁ ነፍሴ ወደ አንተ ትናፍቃለች ነፍሴ ወደ ሕያው አምላክ ተጠማች፤መቼ እደርሳለሁ የአምላክንስ ፊት መቼ አያለሁ?" በማለቱ ወንጌላዊው ዪሐንስም "ጌታ ኢየሱስ ሆይ ና" በማለቱ ናፍቆታቸው ተገለጠ፡፡ ክርስቲያኖች ሆይ በእኒህ ቅዱሳን ውስጥ የነበረው "ሀሳብ" ወይም "ምኞት" አይደለም እንደ እሳት የሚበላ እንደ ውኃ ጥም የሚያቃጥል" ናፍቆት" እንጂ፡፡ መዝ 41(2)፥1-2፣ ራዕይ 22፥20
   በምድረ በዳ የሚሄድ ሰው ከውኃና ከእረፍት በቀር ምን ይናፍቃል? ልብስና ጌጥ ብርና ወርቅ ሌላውም ሁሉ በዚያ በርሃ ሸክም ቢሆን እንጂ ተስፋ አይሆንም፡፡ የዓለም ሀብት ቢሠፈር ጠብታ ውኃ የምትሠጠውን እርካታ የሚመዝን ዋጋ አይኖረውም፡፡ ከጽድቅ ምድረ በዳ በሆነች ዓለም ለሎሎች ብርሃን እንዲሆኑ ተወስኖባችው የዓለምን ርኩሰት ለማየትና ለመስማት ሳይፈልጉ በዚህ የተወሰነላቸውን ጊዜ እንዲኖሩ የተፈረደባቸው ቅዱሳን ነፍሳቸው የዓለምን ርኩስት በመፀየፍና ተወዳጁን ጌታቸውን በመናፈቅ ትጨነቃለች፡፡
የፍቅሩ ማዕበል የሚያማታት መዓዛ ቅድስናው የሚያውዳት ነፍሳቸው በሕያዋን ምድር ቅዱሱን ለማየት ትጠማለች ትናፍቅማለች፤ ቀን ዕረፍት ሌት እንቅልፍ አጥታ ትቃትታለች፡፡ የተጠማ የናፈቀ ለዓይኖቹ እንቅልፍ ለሽፋሽፍቶቹስ እረፍት እንዴት ይሠጣል?
ቅዱስ ጳውሎስ በህይወት መቆየቴ ለእናንተ ይጠቅማል ቢልም የእሱን ናፍቆት ግን ገልጿል፡፡ እውነት ነው የቅዱሳን በእግዚአብሔር ህዝብ መካከል መኖር የእውነተኛ ሐዋርያት ለመንጋው የሚራሩ እረኞች መኖር ለህዝቡ ጥቅም ነው፡፡ በምክራቸው ያፅናኑታል፣በቃላቸው ተስፋውን ከፍ ያደርጉታል፣ በተግሣጻቸው ከኃጢአት በንስሐ ወደ ጽድቅ የመልሱታል፣ በጸሎታቸው መዓትን ያርቁታል በረከትን ያቀርቡለታል ጉድለቱንም ይሞሉለታል፡፡
ሀሰተኞች እየተባሉ እኛን ወደእውነት መምራት፣እየተናቁ እኛን የታወቅን ማድረግ፣ እየተዋረዱ ክብርን ማሠጠት፣ ኃዘንተኞች ሆነው ለእኛ ደስታን መዝራት፤ በድህነት ኖረው ባለጠጎች ማድረግ፣ ሁሉን እያጡ ሁሉን ለእኛ ማሰጠት እየሞቱ የክርስቶስ ሕይወት በእኛ እንዲበራ መጋደል የቅዱሳን ተግባር ነው፡፡ ሰውን ወዳጅ ወደሆነው ጌታ አስክንቀርብና በፍጹም ህሊና ለመታዘዝ እከክንማረክ የመጨረሻውን ውርደት መቀበልና እንደ ዓለም ጥራጊ ጉድፍ ተደርገው መቆጠር የቅዱሳን ደስታቸው ነው፡፡1ቆር 4፥8-13፤ 2ቆሮ6፥4-10፤ዕብ11፥23-28
   ይህም ለእኛ ጥቀም እንጂ ለእነርሱ ምቾት አይደለም፡፡ ናፍቆታቸው ዕረፍታቸው ምቾታቸው ግን ሁሌም ከእርሱ ከከጌታቸው ጋር መኖር ነው፡፡ ሰዎች በተለያየ ምክንያት ሞትን ይመኛሉ የከበረ ሲዋረድ፣ ያገኘ ሲያጣ፣ ያመነ ሲከዳ፣ ያፈቀረ ሲጠላ እንዲሁም በጽኑ ደዌ ሲያዝ፤ የሚወደውን በሞት ሲነጠቅ፣ ከገባበት አጣብቂኝ መውጫ ቀዳዳ አጥቶ ተስፋ ሲያጣ፣ ዙርያው ገደል ሲሆንበት ሞትን ይመኛል፡፡ ግልግል ነው ብሎም ያስባል፡፡ በእርግጥም ከሆነ???
   የቅዱስ ጳውሎስና የሌሎችም ቅዱሳን ከዚህ ዓለም መሰናበትን መናፈቅ ግን ከዚህ እጅግ ይለያል፡፡ በምድራዊ የኑሮው ምቾት አንፃር ካየነው ክቡር ዳዊት እንደ ንጉሥነቱ ሁሉ የተረፈው ነው፡፡ ቅ.ጳውሎስም ለኑሮው በእጁ ደክሞ ለመጠቀም የሚያንስ ሰው አልነበረም፡፡ ደግሞስ ሁሉን ትተው የተከተሉ በፈቃዳቸው አልነበረምን? "…ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት አኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት…" ሲል ለዓለም ምኞት ለሥጋ አምሮት ምውት መሆኑን መግለፁ አይደለምን፡፡
ሐዋርያቱ በዓለም ያወጁት ዓዋጅ "ዓለምን መውደድ ለእግዚአብሔር ጥል መሆኑን ዓለምንና በዓለም ያለውን መውደድ ከፍቅረ እግዚአብሔር እንደሚለይ ዓለሙና ምኞቱ ኃላፊ ጠፊ መሆናቸውንና ፈቃደ እግዚአብሔርን የሚፈጽም ግን ለዘላለም እንደሚኖር አልነበረምን? 1ዮሐ 1፥15-17፣ያዕ 4፥4፤ ገላ 6፥14፤ ዕብ11፥35-38
    ስለዚህ ቅዱሳኑ ከዚህ ዓለም መሔድ የተሻለ እንደሆነ የገለፁት በዚህ ምድር ኑሮ ስላስመረራቸው አግኝተው ስላጡ ከብረው ስለተዋረዱ አይደልም፡፡ " አንዳች የሌለን ስነመስል ሁሉ የእኛ ነው" ማለታቸውን አስታውስ፡፡ ከዚያም በተጨማሪ በምድራዊ ሀብትና ሥልጣን ጥበብና የዘር ግንድ የማይገኝ ታለቅ ሀብት እንደነበራቸው የታወቀ የተረዳ ነገር ነው፡፡ ታዲያ ከዚህ ዓለም መለየትን ለምን ናፈቁ?
፩. ዓለምን መጥላታቸው ነው፡፡ ዓለምን መጥላት ማለት ቅዱስ እግዚአብሔር ለምግበ ሥጋና ለአንክሮ ለተዘክሮ የፈጠራቸውን ፍትረታቱን እና በውስጣቸው ያለውን ተፈጥራዊ ጸጋ አንዲሁም ነዋሪዎቿን መጥላት አይደለም፡፡ ጌታ እግዚአብሔር ከመፍጠር ያልናቀውን እንወድ ዘንድ የተገባ ነውና፡፡
የምንጠላው የምንፀየፈው ርኩሰቷን ግልሙትናዋን ክፋቷን ወዘተ…ነው፡፡ ቅዱሳን መቼም ቢሆን ንፅህናቸው ከርኩሰቷ፤ቅድስናቸው ከግልሙትናዋ፣ የዋሃታቸው ከክፋቷ፣ እውነታቸው ከሀሰቷ፣ ርህራሄያቸው ከጭካኔዋ ጋር ሊስማማ አይችልም፡፡ ታለቁ በታናሹ ብርቱው በድካማው ላይ የሚሠራውን ግፍ መመልከት፤ ከህይወት መንገድ ስተው የሚጠፉትን ማየት፤ በሰነፎችና በኃጢአተኞች አፍ በእግዚአብሔር ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ የሚነገረውን ስድብ መስማት ለቅዱሳን ታላቅ ስቃይ ነው፡፡ ከዚህ ሁለ የሚያርፉት ጽድቅና ቅድስና በነገሠባት ሀሰትና ክፋት በማይሠለጥንባት በዚያች የቅዱስ እግዚአብሔር ከተማ መሆኑን ያውቃሉና መሰናበታቸውን ይናፍቁታል፡፡
፪. ከደካማው ባህርይ መላቀቅን መናፈቃቸው ቅዱሳን ምንም እንኳ በጸጋ እያደጉ በሔዱ ቁጥር ፈቃደ ሥጋቸው ለፈቃደ ነፍሳቸው ቢገዛም፤ እነርሱም ከቅድሰናቸው የተነሣ በአካለ ሥጋ እያሉ ለነፅሮተ ሥሉስ ቅዱስ እስከመድረስ ቢበቁም እንኳ ያለተከፍሎ በእያንዳንዷ የጊዜ ሽርፍራፊ ሁሉ ከተወዳጁ ጌታ ጋር ለመሆን ካላቸው ናፍቆት የተነሣ ማነቆ ከሆነባቸው ምድራዊ ቆይታ መሰናበትን ይሻሉ፡፡ ለቅዱሳን የሚበሉባትና የሚጠጡባት የሚያርፉባትና የሚያንቀላፉባት ሰዓት ሁሉ ፀፀት ናት፡፡ ናፍቆታቸው መብልና መጠጣቸው እረፍታቸውም እደመላእክት እርሱ ጌታቸው እንዲሆን ነውና፡፡ ይህ ደግሞ በአፀደ ነፍስ እንጂ በአፀደ ሥጋ አይሆንም፡፡ ሰው ወደሌለበት ጥልቅ በረሃ መመነናቸው ቅሉ ለዚሁ ነው፡፡ ከዚህ ዓለም የሚሆን ፍልሰታቸውንም መናፈቃቸው ምክንያቱ ይሄው ነው፡፡
  ተወዳጆች ሆይ ቅዱሳን የልባቸው ናፍቆት የነፍሳቸው ጥማት ከሆነው ጌታ ጋር ለመኖርና ህብረት ለማድረግ የዚህን ዓለም ህይወት ረብ እንደሌለው ነገር ቆጠሩት፡፡ ሁሉን ትተው በህይወታቸው ሳይቀር ጨክነው ተከተሉት፡፡ "ለእኛም ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ሥቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ፡፡" እያሉ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ወደ ሞት በፈገግታ ሔዱ፡፡ ሮሜ 8፥18
እኛ ለወደደን እስከሞትም ራሱን አሳልፎ ለሰጠልን ለእርሱ ኃጢአትን፣ ክፋትን፣ ቂምን፣ ረብ የለሽ ደስታን መተው አለመቻላችን ምን ያህል ደካማነት ነው፡፡
ከጌታ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር የመኖርን ደስታ በቅድስና በመኖር የቀመሱት እነርሱ ከዚህ ዓለም ተለይተው ለዘላለም በማይነጥፍ ደስታ ውሰጥ ለመኖር ናፈቁ፡፡
መቼ እንደምንጠራ የሚያውቀውና ሰዓቲቱን የሚወስነው ጠሪያችን ብቻ ነው፡፡ እርሱ ደግሞ የነፍሳችንና የሥጋችን የጊዜያዊውና የዘላለማዊው ዓለም ገዢ ነው፡፡ ከዙፋኑ ፍትህ ከቃሉም እውነተኛ ፍርድ ይወጣል፡፡ ፍርዱንም ይለውጥ ዘንድ የሚችል ከቶም የለም፡፡
የተሻለውን መምረጥ በዚህ አለ፡፡ በጊዜያዊው ለዘላለማዊው በምድራዊው ለሰማያዊው መዘጋጀት፡፡ ክርስቶስን በመመምሰል ቆይቶ ለዘላለም ከእርሱ ጋር ለመኖር መሔድ ወይም…
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር
የካቲት 2005


1 comment:

  1. የመድኃኒት ንግድ ሥራዬን ለማስፋፋት በተጠቀምኩበት ብድር ለመርዳት ሚስተር ቤንጃን ከሚያስፈልጓቸው በላይ አልፈዋል ፡፡
    እነሱ ለመስራት ወዳጃዊ ፣ ባለሙያ እና ፍጹም ዕንቁዎች ነበሩ ፡፡ እኔ ለማነጋገር ብድር የሚፈልግን ማንኛውንም ሰው እመክራለሁ ፡፡ Lfdsloans@outlook.com.WhatsApp ... +19893943740.

    ReplyDelete