Monday, April 8, 2013

ስለጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ (5)


በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁሉን የሚያውቅ የባህርይ አምላክ ስለመሆኑ፤
መግቢያ፡- ባለፉት ሳምንታት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ "ሁሉን ቻይ" አምላክ መሆኑን በተረዳ ነገር አይተናል፡፡ በዛሬው ጹሑፋችን አምላካዊ ባህርያት ከሆኑት አንዱን "ሁሉን ማወቅ" ከመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ በማስደገፍ እናያለን፡፡ የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ምስጢሩን ይግለጽልን!
ሁሉን ማወቅ የእግዚአብሔር የብቻው /የተለየ/ ባህርዩ ነው፡፡ በሰማይም ሆነ በምድር ወይም በውቅያኖስ፣በብርሃንም ሆነ በጨለማ ፣ በቁሳዊውም ሆነ በመንፈሳዊው ዓለም እርሱ የማያውቀው ከእርሱ ተሰውሮ የሚፈጸም አንዳች ስንኳ የለም፡፡ ሁሉንም ከመሆኑ በፊት እንደተደረገ አድርጎ ያውቀዋል፡፡ በጸሎተ ኪዳን እንተፃፈ " እምቅድመ ህሊና ኲሎ የአምር፣ ወእምቅድመ ህሊና ይፈትን" ከህሊና አስቀድሞ ያውቃል፣ ከሀሳብም ቀድሞ ይመረምራል፡፡ ዓለምን ጅማሬው ላይ ሆኖ ፍፃሜውን ያውቀዋል፡፡ በአጭር ቃል ከእርሱ ምንም ምን አይሠወርም የክፍዎችንም ሆነ የበጎዎችን ምክር ያውቃል፣ የጠቢባንንም አሳባቸውን ይመረምራል፡፡ ከመሆኑ አስቀድሞ እንጂ ከተደረገ በኋላ ተመራምሮ በነገሩ የሚደርስ አይደለም፡፡ በመሆኑም አኛንም ማንም ከሚያውቀን ይልቅ ከራሳችንም በላይ ያውቀናል በመጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ተብሏል፡፡
1ሳሙ 2፥3 " አትታበዩ በኩራትም አትናገሩ፡ እግዚአብሔር አዋቂ ነውና…"
1ኛ ዮሐ 3፥20 " እግዚአብሔር ከልባችን ይልቅ ታላቅ ነውና ሁሉንም ያውቃል"
ይህ እንዲህ ከሆነ "ሁሉን አዋቂነት" የሚለው ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀፀል ይችላል ወይ? የሚለው ጥያቄ ነው፡፡ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ምላሽ "በትክክል" የሚል ነው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ እነሆ፡፡
ማቴ9፥1-8 ጌታ እየሱስ ክርስቶስ በአልጋ የተኛ ሽባ ወደ እርሱ ባመጡ ጊዜ ሽባውን"አንተ ልጅ ኃጢአትህ ተሰረየችልህ" አለው፡፡ ከጻፎች ግን አንዳንዶቹ በልባቸው ይህስ ይሳደባል አሉ፡፡ ኢየሱስም አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አለ ስለምን በልባችሁ ክፉ ታስባላችሁ?...
ማቴ 12፥15 ጌታችን በሰንበት ስለፈወሰ ፈሪሳውያን ሊገድሉት ሲማከሩ ምክራቸውን አውቆ ከዚያ ፈቀቅ አለ ይላል፡፡
ማቴ 12፥22-27 ሕዝቡ በአጋንንት ላይ ባለው ሥልጣን ሲደነቁ ፈሪሳውያን ግን በአጋንንት አለቃ በብዔል ዜቡል አጋንንትን ያወጣል በማለት ሲያስቡ ኢየሱስ ግን አሳባቸውን አውቆ እንዲህ አላቸው እርስ በርሷ የምትለያይ መንግስት አትፀናም…
ማቴ 17፥24-27 ቀረጥ ሰብሳቢዎች ጰጥሮስን በውጭ አግኝተው መምህራችሁ ግብር አይገብርምን? ብለው ሰለጠየቁት ጴጥሮስ ይህን ሊናገር ወደ ቤት ሲገባ አስቀድሞ የሆነውን አውቆ ዓሣ አጥምዶ ያገኘውን እንዲከፍል ነግሮታል፡፡
ሉቃ 5፥1-11 ቅዱስ ጴጥሮስ ሌሊቱን ደክሞ ያልሆነለትን በጌታችን ትዕዛዝ ብዙ ዓሣ በመያዙ ቢደሰትም በታላቅ ፍርሃት ጌታን "እኔ ኃጥአተኛ ሰው ነኝና ከእኔ ተለይ" ብሎታል፡፡ መተርጉማን ይህን የቅዱስ ጴጥሮስን ቃል ሲፈቱት የባህሩን ውስጥ እንዲህ ያወቀው የእኔንማ ልብ እንዴት ይመረምረው ብሎ እንደፈራ ያትታሉ፡፡
ሉቃ 7፥36-50 መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በስምዖን ፈሪሳዊ ቤት ለምሳ በተቀመጠበት ወቅት ባለ ሽቶዋ ማርያም እግሩን እየሳመች በእንባዋ እያጠበችና በፀጉርዋ እያበሰች ሽቶ ቀብታ ሰለኃጢአቷ ሥርየት በአርምሞ ስትማፀ ስምዖን ፈሪሳዊ አይቶ ይህስ ነብይ ቢሆን ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን እንደሆነች እንዴትስ እንደነበረች ባወቀ ነበር ኃጥአተኛ ናትና ብሎ በልቡ አሰበ፡፡ለዚህ ሰው የልቡን አውቆ  ምን ዓይነት አስደናቂ መልስ እንደሰጠው ቃሉን አንብብ፡፡
ሉቃ 8፥43-48 12 ዓመት ደም ይፈሳት የነበረች ሴት የነበረች ሴት ጌታን ህዝቡ እያገፋው ሳለ ተሰውራ የቀሚሱን ዘርፍ በመንካቷ ተፈወሰች ጌታም ማን ነው የነካኝ ብሎ ሲጠይቅ ሐዋርያት ህዝቡ ይገፉሃል ማነው የነካኝ ትላለህን? ሲሉት አንድ ሰው ዳሶኛል ኃይል ከእኔ እንደወጣ እኔ አውቃለሁና ብሎ ነው የመለሰው ሴቲቱም እንዳልተሠወረች ባየች ጊዜ እየተንቀጠቀጠች መጥታ በፊቱ ተደፋች የተደረገላትንም በህዝቡ ሁሉ ፊት መሠከረች፡፡
ሉቃ 22፥31-34 ጌታችን እንደሚያዝና ሁሉም ጥለውት እንደሚሸሹ በተናገረበት ምሴተ ሐሙስ ቅዱስ ጴጥሮስ ሌሎች ቢክዱህ እኔ አልክድህም ብሎ ለሠጠው የትምክህት መልስ" ዶሮ ሳይጮህ ሦስት ጊዜ እንደሚክደው ቀድሞ ነግሮታል፣ ይኸውም እንደቃሉ ተፈፅሟል፡፡
ዮሐ2፥5 " ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር፤ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር፡፡ ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና፡፡
ዮሐ 1፥47-50 ፊልጶስ ናትናኤልን ጋብዞ ወደ ጌታችን ባመጣው ሰዓት ጌታ "በልቡ ተንኮል የሌለበት የእስራኤል ስው እነሆ" በማለቱ ናትናኤል ከወዴት ታውቀኛለህ? ቢለው ፊልጶስ ሳይጠራህ ከበለስ በታች አየሁህ የሚል መልስ ሲሰጠው" መምህር ሆይ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፤አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ" በማለት እርሱ ሁሉን አዋቂ አምላክ ወልደ አምላክ መሆኑን መስክሯል፡፡
ዮሐ4፥1-መጨረሻ  በተፃፈው ፍፁም የሚመስጥ ታሪክ ሳምራዊቷ ሴት ለሀገሯ ሰዎች ከጌታችን ጋር ስለነበራት ቆይታ ስትገልፅላቸው ወደ እርሱ እንዲመጡም ስትጋብዛቸው "ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ…" ብላለች ቁጥር 29
ዮሐ6፥15 እንጀራ በልተው ሲጠግቡ እርስ በርሳቸው ከሆነስ አይቀር ስንራብ እያበላ ፣ስንጠማ እያጠጣ፣ስንታመም እየፈወሰ፣ስንሞት እያሰናዳ ቢገዛን መልካም በሆነ ኑ እናንግሠው ብለው ያሰቡትን አውቆ ከአጠገባቸው ፈቀቅ ብሎ ወደ ተራታ ወጣ ይላል፡፡
ዮሐ11፥1-መጨረሻ ፡- በቦታው በአካል ባይገኝም ስለአልዓዛር መታመምና መሞት ቀድሞ ለሐዋርያት ነግሯቸዋል፡፡
v  ጌታችን ስለሞቱና ትንሣኤው አስቀድሞ ተናግሯል፡፡
ማቴ 24፥1-መጨረሻ፡- የዓለም መጨረሻና የዳግም ምፅዓቱ ምልክቶችን አስቀድሞ ተናግሯል፡፡        ዮሐ16፥29-30 ሐዋርያት"እነሆ አሁን በግልጥ ትናገራለህ፣በምሳሌም ምንም አትናገርም ሁሉን እንድታውቅ ማንምም ሊጠይቅህ እንዳትፈልግ አሁን እናውቃለን፡፡
ዮሐ21፥15-17 በጥብርያዶስ ባህር ዳርቻ ጌታችን ከስምዖን ጴጥሮስ ጋር በነበረው ቆይታ "ትወደኛለህን?" ብሎ ሦስት ጊዜ ለጠየቀው ጥያቄ የሰጠው የመጨረሻ ምላሽ "ጌታ ሆይ አንተ ሁሉን ታውቃለህ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ " የሚል ነው፡ በዚህም ሁሉን አዋቂ መሆኑን አስረግጦ መስክሯል፡፡ በመቀጠል ጌታችንም ቅዱስ ጴጥሮስ በኔሮን ቄሣር ዘመን በምን ዓይነት ሞት እግዚአብሔር ያከብር ዘንድ እንዳለው ነግሮታል ይህም ሁሉን አወቂ መሆኑን ያስረገጠበት መንገድ ነው፡፡
ራስን መመዘኛ /መመርመርያ/ ጥያቄ!

.የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አዋቂነቱ በእኔ ሕይወት ውስጥ ያለው ተፅዕኖ ምን ያህል ነው?
ለ. በእርግጥ እግዚአብሔር ሁሉን አዋቂ መሆኑን በእውነት አምናለሁ?
. እግዚአብሔር ከሁሉን አዋቂነቱ ወሰን ተሠውሬ ኃጢአት ሠርቼ አውቃለሁን?
መ. ቅዱስ እግዚአብሔር / ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ / ከልቤ ጋር ያለው ግንኙነት ምን ያህል ነው? እንዴትስ እረዳዋለሁ?

v  በሀገር ውስጥ ላላችሁ ለጥያቄዎቹ መልስና ሀሳባችሁን በሪፖርት(በወረቀት) በጉባኤ ቀን ትሰጣላችሁ፡፡
ይቆየን!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

No comments:

Post a Comment